2020 ጁላይ 27, ሰኞ

እኔና ግድቡ

. . . ‘ግድቡ የኔ ነው’ የሚል አቋም ይዤ አላውቅም. . . ‘ብላክ ላይቭስ ማተርስ’ም አላልኩም። የግድቡና የጥቁር ህይወት ጉዳይ የሚገናኝ ቢሆንም እንደነዚህ አይነት ባለመንሰላል ቃላት (ሃሽታግ) ብዙም አልጠቀመም - የጅምላ አስተሳሰብ ውስጥ የሚዘፍቁኝ ይመስለኛል - ሃሽታጋም መሆን አልፈልግም። እንደዚህ ብልም ግን ግድቡ ላይ አያገባኝም ማለት አይደለም እንደውም በዚህ ግድብ የተነሳ የደረሰብኝን ላጋራችሁ ነው የተነሳሁት። እስከዛሬ ለምን እንዳልጻፍኩት ለራሴም ግራ ነው።

የዛሬ ዓመት ከምናምን ለስራ ጉዳይ ለመጀምሪያ ጊዜ ከሃገር ወጣሁ። በገዛ የሃገሬ አየር መንገድ አውሮፕላንና በገዛ የሃገሬ ቆነጃጅት የበረራ አስተናጋጆች ቀለም አልባ ቆዳ ያላቸው ሰዎች /ነጮች/ በሁሉም ነገር ቅድሚያ ሲሰጣቸው ሳይና ባረፍኩበት ሆቴል ውስጥ ሊፍት ስሳፈር ያጋጠሙኝ ሰዎች አንዳች ዘራፊ እንደገጠማቸው አይነት ነገር ሲጨማቀቁ ሳይ - ለመጀመሪያ ጊዜ ጥቁርነት ተሰማኝ፣ አሃ ለካ ጥቁር ነኝ አልኩኝ፣ ሬሲስት ሃገሮች ውስጥ የሚኖሩ ሰዎች ለካ የዕለት ተዕለት ኑሮዋቸው እንዲህ ነው አልኩ. . . ጠቆርኩ። ይኼኔ እኮ እነዛ የበረራ አስተናጋጆችም ‘ብላይክ ላይቭስ ምናምን’ ብለው ለጥፈዋል - ቲሽ!

ጦሰኛው ግድብ ጋር ከመድረሴ በፊት ላንድ ሎክድ አገር ውስጥ የመኖር አንዱን መዘዝ ላውጋችሁ። ከውቅያኖስ ወይም ከባህር የራቀ ህዝብ በዛ ውስጥ የሚገኙትን እንስሳት ከመብላትም በእጅጉ ይርቃል። እኔም እንደአብዛኛው የባህር በር አልባ አገር ሰው ከባህር ለሚገኙ ምግቦች እንግዳ በመሆኔ ‘ሽሪምፕ’ የሚባል ነገር ለመጀመሪያ ጊዜ ቀመስኩ።

ወደ ሆቴሌ እንዲያደርሰኝ የተመደበው መኪና አርፍዶ በመምጣቱ ‘ይኼ ሰውዬ ሐበሻ ነው ወይም ሌላ አይነት ጥቁር መሆን አለበት’ እያልኩኝ እያለ የሆነ ኮርስ ያስተማረንን ህንዳዊ የመሰለ ሰው ከች አለና ‘ሚስተር ተማም’ አለኝ በቲፒካል የህንድ አክሰንት። እኔም እንደጥቁር ራሴን አሳንሼ እንደነበር የገባኝ ሻንጣዬን ተቀብሎ መኪናው ላይ ለመጫን ሲል አይሆንም ብዬ ስግደረደር ነበር። የካምፓኒው ፕሮቶኮል ስለሆነ የእሱ ስራ እንደሆነ ሲነግረኝ ነው ራሴን ቆንጠጥ አድርጌ ደረቴንም ነፋ አድርጌ ሻንጣዬን የሰጠሁት። አጅሬ የማርፍበትን ማርዮት ሆቴልም በትክክል ለማወቅ ተቸግሮ ሲያሸከረክረኝ ቆየ። እኔ ከሱ ተሻልኩና ሃምዳን ቢን ሞሐመድ ስትሪትን በካርታ ላይ አገኘሁት። ሰው እየጠያየቀም ቢሆን መድረስ ከነበረብኝ ሰዓት አስረፍዶ አደረሰኝ።

ክፍሌን ተረክቤና ተሽሞንሙኜ የሄድኩበትን ጉዳይ እራሴን በማስተዋወቅ ‘ሀ’ ብዬ ልጀምር ተዘጋጀው። ከሰላሳ ምናምን ሃገራት የመጡ የተለያዩ ሰዎች ያሉበት አቀባበል እየተጠናቀቀ እንደኔው ያረፈዱ ሁለት ሰዎች እራሳቸውን እያስተዋወቁ ደረስኩና ወዲያው እኔም ስሜን ከሃገሬ ጋር አድርጌ መጥራቴ የፈጠረብኝን ልዩ ስሜት እያጣጣምኩ እራሴን አስተዋወቅኩ። ከካራ ወጥቼ ኡራኤል አካባቢ መኖር ስጀምር ራሴን የካራም የኡራኤልም ልጅ ነኝ አልልም ነበር፣ ጅማ ዩንቨርሲቲ የተመደብን ጊዜ ይመስለኛል አዲስ አበባ የሚለውን ቃል መጠቀም የጀመርኩት . . . አንድ ቦታ ብዙ ጊዜ ስንሆን በቃ ነገር ዓለሙ ሁሉ ያ ቦታ ብቻ አይነት ነገር ይሆንብን የለ?! እኔም ከኢትዮጵያ የምትለዋን ባገኘኋት አጋጣሚ ሁሉ በኩራት ከማለቴ የተነሳ በመጣበት ሃገር ስም ስጠራ የነበርኩት እኔ ብቻ ሳልሆን አልቀርም።

ትውውቁ እንዳለቀ ከዛ ሁሉ ነጭ መሃል የነበሩት እናቴን የሚያካክሉና አክስቶቼን የሚመሳስሉ ሶስት ጥቁር ሴቶች አንድ ላይ ፎቶ መነሳት ጀመሩ እኔም ምን እንደጠራኝ አላውቅም አራተኛ ሄጄ ልጥፍ አልኩኝ። የሴኔጋል፣ የጋና እና የትሪኔዳድ ተወካዬች ነበሩ - እኔም ብቸኛው ጥቁር ወንድ ነበርኩ። ያቺ የበረራ አስተናጋጅ የስራዋን ይስጣትና (የሚያበር ያብርራት፣ የሚያስተናግድ ያስተናግዳትና) የረባ ምግብ እንዳላገኝ ለኔ ዋናውን ምግብ ሳታቀርብ ነጩን ሼባ መጠጥ ካልጋበዝኩህ የሚመስል ጥያቄ ስታቀርብለት ሳይ ዘጋኝ በቅጡ አልበላሁም ነበርና ሪሴፕሽኑ ላይ ከነበረው ምግብ አይቼ የማላውቀውን መርጬ ማጫወት ጀመርኩ። በዚህ ጊዜ የባሩ ባንኮኒ ላይ ተፈናጥጬ ምግቤን በወይን እያወረድኩ ከኒውዮርክ ከመጣች ሴትዮ ጋር የጦፈ ወሬ ውስጥ ገባሁ። በመሃል አንገቴና ጉንጬ ዙሪያ የሚያሳክክ ነገር ያሸማቅቀኝ ጀመር። ‘ታጥቤ ልብስ ቀይሬ ነው የወጣሁት።’ ‘ሳሙናው አልተስማማኝም ይሆን?’ ‘ኸረ እዚህ አገር አይታከክም!’ ‘ከአንድ ብርጭቆ በላይ አልጠጣሁ. . . ደሞ ወይን ያሳክካል እንዴ?. . . ለዛውም የዚህ ሃገር?!’

በጠዋት ተገናኝተን ቁርስ አንድላይ በልተን በባስ እንደምንወሰድ ተነገረንና ሁሉም እረፍት ሊያደርግ ወደየ ክፍሉ ሲገባ እኔም ለጓደኞቼ ያለሁበትን እያሳየሁ ላቅራራ ዋይፋይ እየፈለግኩ እያለ አየር አጠረኝ፣ ሳል በሳል ሆንኩኝ፣ ሰውነቴን የሚያሳክከኝ ነገር እየባሰ መጣ (ያኔ ኮቪድ ቢኖር መቶ በመቶ እሱ ነው ነበር የምለው). . . ብቻ ማሳል፣ ብቻ ማከክ፣ ብቻ አይን መብላት. . .  የምሆነው ነገር አሳጣኝ ይባስ ብሎ ከፍተኛ ቁርጠት። ሆድ ቁርጠት ለአፍሪካዊ ብርቅ አይሆንም እንደዚህ ግን ስለት የመሰለ ቁርጠት ገጥሞኝ አያውቅም።

ወደ ክፍሌ ስበር ሄድኩኝ። መስታወቱ ውስጥ ያለሁት እኔ መሆኔን ለማመን ያስቸግራል። በብዙ ነገሮች ቀልቶ የሚያውቀው አይኔ ነጩም ነጭነት ጥቁሩም ጥቁርነት የመረራቸው ይመስል እንዲህ ቀልተው ግን አያውቁም (ሬድ ላይቭስ ማተር ብለው ነበር)… 

. . . ይቀጥላል . . . 

2016 ኤፕሪል 11, ሰኞ

ንጹህ አቅም


ሰላም ወዳጆች
ይህች ጦማር ታዳሚዎችዋን ለማንቃት ተናስታ እራሷ ተኝታ ብትከርምም ከአሁን በኋላ በተከታታይ ከ ዲፓክ ቾፕራና ሌሎች ጸሃፍት በሚቀነጨቡ ጽሁፎች ልንቀሰቅሳት ወደናል። በማህበራዊ ገጥ የቀረበ የመጀመሪያ ትርጉም ስራዬ ነውና ማንኛውንም አይነት አስተያየት ከአንባቢ ለመቀበል በጉጉት እጠብቃለሁ - በተለይ ደግሞ ስራዎቹን ቀድመው አንብበው ከነበሩ ታዳሚያን። ቅድሚያ ጦማሯን እንቀስቅስ ከዛም እራሳችንን... መቀሳቀስም አይደል አላማችን?። የመጀመሪያዋን ማንቂያ እንኋት ‘ ንጹህ አቅም’! እዚህ ጋር ንጹህ ስንል የምንጠቀምበት ቃል ተፈጥሯዊ ንጽህናን በዓለማዊ አኗኗር ያልበለዘ ቅድስናን ለማመላከት ሲሆን የሰው እውነተኛ ማንነት ላይ የሚቀርቡ ሃሳቦችን ከሐይማኖቶች ጋር በማይጣሉ መልኩ ሳይሆን ሁሉም ሐይማኖተኛ ሰው ከየራሱ ሐይማኖት አስተሳሰብ አንጻር ሊያየው በሚችለውመልኩ የሚቀርቡ ይሆናሉ። በዚህም አቀራረብ ዙሪያ የማስከፋው ምንም አይነት አካል የሚኖር እንደሆን አለመከፋትን መምረጥ የዛ አካል ድርሻ መሆኑን በማመላከት አስቀድሜ ይቅርታ እጠይቃለሁ።

ንጹህ አቅም

 ዲፓክ ቾፕራ


የመጀመሪያው የስኬት መርህ ‘the law of pure potentiality’ ወይም እዚህ እንደምንጠቀምበት ትርጉም የንጹህ አቅም መርህ ነው። ይህ መርህ የተመሰረተው እኛ ሰዎች በመሰረታዊው መገኛችን ማንነታችንንጹህ ንቃት የመሆናችን ሃቅ ላይ ነው። ንጹህ ንቃት ደሞ ንጹህ ብቃት ወይም አቅም ነው ይህም የአማራጮች እና ማለቂያ የሌለው የፈጠራ ችሎታ መገኛ መስክ ነው። ንጹህ ንቃት የመንፈሳዊ ማንነታችን መገለጫ ከመሆኑም ውጭ ማለቂያ የሌለውና ያልታሰረ ንጹህ ደስታም ነው። ንጹህ እውቀት' ገደብ የለሽ ፀጥታ' አይበገሬነት' ጥራትና ሃሴት የንጹህ ንቃት መለያዎች ናቸው። ይህም የሰው ልጆች መሰረታዊ ተፈጥሮ ወይም ማንነት ነው።
ሰው መሰረታዊ ተፈጥሮውን ወይም እውነተኛ ማንነቱን ሲያውቅ ያ ዕውቀት በራሱ ማንኛውንም ህልሙን ማሳካት የሚያስችል አቅም ይሆናል ምክኒያቱም ሰው ያለ የነበረና የሚኖረው ዘላለማዊ ችሮታና ገደብ የለሽ አቅም ነው። የንጹህ አቅም መርህ ያልነው እንግዲህ የአንድነት መርህም ሊባል ይችላል ምክኒያቱም ህልቆ መሳፍርት ከሌለው ተፈጥሮ ላይ ከሚስተዋለው ልዩነት በስተጀርባ ያለው የመንፈስ አንድነት ነውና። በሰውልጅ እና በዚህ የሃይል መስክ መካከልም ምንም የሚለያይ ነገር የለም። ሰው እውነተኛ ተፈጥሯዊ ማንነቱን ባገኘ ቁጥር ወደ ንጹህ ብቃት ወይም አቅም እየተጠጋ ይሄዳል።
ራስን መሆን ‘self-referral’ ማለትውስጣዊ  የማነጻጸሪያ ነጥባችንን ከራሳችን መንፈስ ውጭ ባሉ ነገሮች ሳይሆን መንፈሳችን ላይ ማድረግ ማለት ነው። የዚህም ተቃራኒ ነገሮችን ማንጸሪያ ማድረግ ‘object-referral’ ሲሆን በዚህም ምንግዜም ከኛ ውጭ ባሉ እንደ ሁኔታዎች' ምህዳሮች'ሌሎች ሰዎችእንዲሁም በነገሮች ተጽእኖ ስር እንውድቃለን። ነገሮችን ማንጸሪያ በምናደርግበት ጊዜ የሌሎችን እውቅናና ይሁንታ ያለማቋረጥ እንፈልጋለን፤አስተሳሰባችንና ባህሪያችንም መልስ በመፈለግ ላይ የተጠመደ መሆኑ ይህን መንገድ ፍርሃት ላይ የተመሰረተ ያደርገዋል።
ነገሮችን ማንጸሪያ በምናደርግበትጊዜ ነገሮችን ለመቆጣጠርም አስገዳጅ ፍላጎት ይሰማናል። ይህ አስገዳጅ ፍላጎት ውጫዊ የሆነ ሃይልን ለማግኘት የሚሰማን ሲሆን  እውቅናን ወይም ይሁንታን ለማግኘት' ነገሮችን በቁጥጥራችን ስር ለማድረግ እንዲሁም  ውጫዊ ሃይልን ለማግኘት የሚሰሙን አስገዳጅ ፍላጎቶች ሁሉ ፍርሃት ላይ የተመሰረቱ ይሆናሉ። የዚህ አይነቱ ሃይል ንጹህ አቅም ወይም እራስን የመሆን ሃይል አይደለም ጭራሹንም እውነተኛ ሃይል  አይደለም። እራስን የመሆንን ሃይል ስናራምድ ፍርሃት ይጠፋል' መቆጣጠር የምንፈልገው ነገር አይኖርም' የማንንም የምንንም እውቅናም ሆነ ይሁንታ ወይም ውጫዊ ሃይል ለማግኘት  አንታገልም።
ነገሮች ማንጸሪያ ሲሆኑ ውስጣዊ ማንጸሪያ ነጥባችን ኢጎ ብለን የምንጠራው ሃሰተኛው ማንነታችን ነው። ኢጎ የራስ ምስል ነው፤ ማህበራዊ ጭምብል ነው፤ የምንጫወተው ሚና ነው። ማህበራዊ ጭምብላችን ሁሌም ይሁንታና እውቅናን እንዲሁም መቆጣጠርን የሚፈልግ ሲሆን በፍርሃት የሚኖር በመሆኑም የሚያቆየውን ሃይል የሚፈልግ ነው።
እውነተኛው ማንነታችን ሙሉለሙሉ ከነዚህ ነገሮች የጠራ ሲሆን በሂስ የማይኮስስ' በፈተና የማይሸበር እና ከማንም የበታችነት የማይሰማው እንደውም ሁሉም ሰው በመሰረቱ አንድ መሆኑን፤ በተለያየ ሰውነት ውስጥ ያለ አንድአይነት መንፈስ መሆኑን ስለሚረዳ በአጉል ኩራት ሳይያዝ ከማንም የበላይነት አይሰማውም።
ነገሮችን ማንጸሪያ በማድረግና እራስን ማንጸሪያ በማድረግ መሃል ያለው መሰረታዊ ልዩነት ይህ ነው። እራሳችንን ማንጸሪያ ስናደርግ በፈተና የማይበረግገውን' ሁሉንም ሰው የሚያከብረውንና ከማንም የበታችነት የማይሰማውን እውነተኛውን ማንነታችንን እናገኛለን። እራስን የማወቅ ሃይል ትክክለኛው ሃይል ነውና።
በሌላኛው በኩል በነገሮች ማንጸሪያነት የተመሰረተ ሃይል የውሸት ሃይል ነው። ኢጎ ወይም ሃሰተኛው ማንነታችን ላይ የተመሰረተ በመሆኑም  የሚቆየው የምናነጻጽርበት ነገር እስካለ ድረስ ብቻ ነው። ማዕረግ ያለው ሰው ቢሆን' የሃገር ፕሬዝዳንትም ሆነ የተቋም የበላይ ኅላፊ ወይም ብዙ ገንዘብ ያለው ባለጠጋ የሚደሰትበት ሃይል ከማዕረጉ' ከስራው ወይም ከገንዘቡጋር አብሮ ጠፊ ነው። ኢጎ ላይ የተመሰረተ ሃይል እነዚህ ነገሮች እስካሉ ድረስ ብቻ የሚቆይ ነው። ማዕረጉ' ስራው ወይም ገንዘቡ በጠፉ ጊዜ የሚጠፋ ሃይል ነው።
ራስን በመሆን የሚመጣው ሃይል የራስ ሃይል ግን እራስን ከማወቅ የሚመነጭ በመሆኑ ቋሚ ነው። ይህም የራስ ሃይል ያልነው የሚከተሉት መገለጫ ባህሪያት አሉት። ሰዎችን' የምንፈልጋቸውን ነገሮችንና  ሁኔታዎችን ሁሉ ወደኛ ይስባል። ይህም በክብር ከመገለጥ የሚመጣ መለኮታዊ ድጋፍ በመሆኑ የተፈጥሮ ህግ ድጋፍ ተብሎም ይጠራል። ሃይላችንም ከሰዎች ጋር በመጣመራችን የምናጣጥመው ሰዎችም ከኛ ጋር በመጣመራቸው የሚያጣጥሙት አይነት ነው። ሃይላችን የጥምረት ነው፤ ይህም ጥምረት ከፍቅር የመጣ ነው።

ይቀጥላል ...

ሰይፈ ተማም 2008


2015 ሜይ 31, እሑድ

ምን ችግር አለው?


. . . አሁን እስቲ ዝምብለው ሲያካብዱ ነው እንጂ ኢህአዲግ ይህን ሁሉ ሽርጉድ ብሎ ያዘጋጀውን ሰርግ ቢሞሸርበት ምን ችግር አለው?
ህዝቡ በነቂስም ሆነ በቀሚስ ወጥቶ ቢመርጥ ባይመርጥ ምን ችግር አለው? የአፍሪካ ህብረትን የሚያክል ግዙፍ ተቋም(በህንጻው እርዝማኔ ነው) ስራ አስፈትተን ታዘቡን ባንል ምን ችግር አለው? . . . ችግር የለውም . . .
አንዳንዶቻችንን እንደሆነ አይነት በሽታ የተጠናወቱን አንዳንዶቻችንን ደሞ ያማረሩን የዘመኑ አነጋገሮች ቢኖሩ “ምን ችግር አለው?” እና “ችግር የለውም!” ናቸው። የሚገርመኝ ነገር የመጀመሪያው ጥያቄያዊ ዓረፍተ ነገር ቢሆንም በተጠቃሚዎቹ ድምፀት እና መልስ አለመጠበቅ የተነሳ እንደጥያቄ ሲቀርብ አላስተውልም። ለ”ምን ችግር አለው?” እንደመልስ ባይቀርብም መልስ የሚመስለው “ችግር የለውም” በብዛት ጥቅም ላይ የሚውለው በቸልተኝነት፣ በመሰላቸት፣ በችኮላና መሰል መንገዶች ነው  -ለዛውም በጠያቂዎቹም ሳይቀር። አሉታዊ አጠቀቃቀሙ እና ተፅዕኖው እየጎላ መጣ እንጂ “ችግር የለውም!” የሚለውን አነጋገር መጠቀም እንኳን ችግር የለውም(አመለጠኝ)። ብዙዎቻችን የማናውቃት ጎረቤታችን ኬኒያን ጨምሮ የስዋሂሊ ተናጋሪዎች “ሃኩና ማታታ” የሚሏት እንደውም ከአፍሪካ ውጪ ሁላ ታዋቂ የሆነች ሃረግ አለቻቸው እዚም እዛም የሚጠቀሟት ትርጉሟ “ችግር የለም” ነገር ነው። አጠቃቀሙም በጣም አዎንታዊ ይላሉ - እኛ “ሁሉ ሰላም” እንደምንለው አይነትም ሊወሰድ ይችላል። የኛዋ ችግር የለውም ግን ጭራሽ አድማጩ ያላሰበውን ችግር ታሳስባለች። ችግር በሌለበት ችግር የለውም። ችግር በችግር(ፕሮብሌም) ተከበንም ችግር የለውም። እውነቱን ልንገራችሁና እኔ እንደውም ከዚህ በኋላ አንድ ሰው ሊያሳምነኝ “ችግር የለውም” ባለ ቁጥር ችግር ብቻ ሳይሆን አደጋ ነው የሚታየኝ - “አደጋ አለው” አለች አሉ ያቺ ሴትዮ።
ቆይ ግን እነዚህን አባባሎች በስፋት እየተጠቀምን መምጣታችን ችግር ምን ያህል እንደተተበተበብን ነው እሚያሳየው ወይስ ችግርን ምን ያህል ተቆጣጥረንና ቀለል አድርገን መመልከት ለመቻል መብቃታችንን? ይህን ጉዳይ የስነ-ችግር ባለሞያዎች ጥናት ቢያደርጉበት ችግር የለውም።
አንድን ነገር ለማድረግም ሆነ ላለማድረግ የግድ ችግር መኖር ወይም አለመኖር አለበት እንዴ ጎበዝ? እርግጥ ነው ችግር መፍትሔን ያመጣል፣ ችግር ብልሃትን ይፈጥራል ወዘተ ወዘተ... አንድ ነገር ልትሰራ ስትል “ቆይ በኋላ ብትሰራው ምን ችግር አለው?” ይልሃል ድራፍት ካልጋበዝኩህ የሚል ጓደኛህ። ምናልባትም ካንተ በላይ የተማረ ነውና ያሉትን ችግሮች ማስረዳቱ ስድብ መስሎ ይሰማህ ይሆናል። ወይም ደሞ ትርጉሙ ያንተ ግብዣ ቀረ አልቀረ ፣እንደውም ካንተጋር መጠጣት አይመቸኝም ምናምን ምናምን . . . ምናምን ይመስልህና አንተም “አንድ ሁለት ብጠጣ ችግር የለውም” ትለዋለህ እራስህን ከዛም እሱኑ - ያለውን ችግር ሁሉ ስታውቀው።
. . . ሴትዮዋ መንገድ ዳር ሚኒባስ ታክሲው ሁሉ ሞልቶ እየመጣ አልጭን ብሎ ሲያልፋቸው ቆይተው በመከራ የተገኘ አንድ ሚኒባስ ሳ አጠገባችው መጥቶ ገጭ “ጎሽ ልጄ ተባረክ አንተ ትሻላለህ” ብለው የጀመሩትን ምርቃት ሳይጨርሱ እንደ አነባበሮ አንዱ ባንዱ ላይ የተነባበረወን ተሳፋሪ አይተው መለስ ቢሉ ረዳት ሆዬ ጭራሽ እያዋከበ “ግቡ እንጂ ማዘር” ይላል “ምን ላይ ነው እምገባው?”
“ችግር የለውም ይጠጉሎታል”
“የት ነው ሚጠጉት? ተው ለኔ አይሆንም”
“ኧረ ችግር የለውም ማዘር ኑዚ” የዘረጋውን እጁን እንኳ ለማሳረፍ ያልበቃች ቦታ እየጠቆመ።
ሴትዮዋም አሉ “የዘንድሮ ልጆች ችግር የለውም ችግር የለውም እያላችሁ ነው ችግር ያመጣቹብን”
ኧረ ማዘሮችና ፋዘሮች ደሞ የዘንድሮ ልጅ ምናምን እያላችሁ አትንቆሩና እንዴ እኛ በስንቱ እንነቆር። ደሞስ ምን አርጉ ነው እሚሉን? መሞት እንኳን አልተፈቀደልንም እኮ። የደርግ ዘመን ወጣት ነጭ እና ቀይ ሽብር እየተፋፋመበት ይረሸን ነበር። የሚታገለውም ለውጥ ወይም ሞት በሚል አይነት መንፈስ እንደነበር የስሚ ስሚ ሰምተናል። እኛ ግን ቀለሙ ያልታወቀ ሽብር እየተፋፋመብን ድንዝዝ፣ ክልትው፣ ኩምሽሽ፣ ሁሉን እርስት፣ በአካልም በመንፈስም ካገር ሽሽት ብለን አለን። እናም አሁን ግርም እያለን እኛ የመረጥነው ነው እሚመራን እሱ የመረጠንን ነው እሚመራው? ተወካዮች ምንድነው? ምርጫ ምንድረነው? ባንመርጥ ምን ችግር አለው?(ባንመርጥ የሚለው ቃል ቢጠብቅ ባይጠብቅ ምን ችግር አለው?) ምናምን ልንል ይቃጣናል። ደሞ ብንልስ ምን ችግር አለው?



ሰላም!

2015 ሜይ 19, ማክሰኞ

ንቃት

ንቃት

ይህ ለማንቂያ ደውልነት የተዘጋጀ ጦማር ነው፡፡ እነሆ ነገር ሁሉ መልካም ሆኖ ይህ ጦማር ይፈጠር ዘንድ ተችሏል፡፡

ንቃት ንቃት ንቃት… ከምን?.... ካለንበት አውቆ የመተኛት አባዜ ነዋ፡፡ ምንም እንኳ አውቆ የተኛ ሲቀሰቅሱት ባይሰማም… ቆይ ቆይ ግን ማን የነቃ ሆኖ ማንን ሊቀሰቅስ ነው…? በዚ ከወሰድነውማ አኔም ነቄ እናንተም ነቄ፡፡ ነቄ ለ ነቄ አይደባለቄ እንበል ይሆን?

ሞቲቬሽን የሚሉትን ቃል መነቃቃት በሚል በብዙ ሰዎች ሲተረጎም ከማስተዋል ብሎም አዌክኒንግ የተሰኘው ጥልቅ ትርጉም ያለው የእንግሊዘኛ ቃል መንቃት ወይም ማንቃት በሚል በአቻነት ጥቅም ላይ ሲውል ከመታዘብ የተገኘ ስያሜ ነው፡፡
ይህም በእርግጥ የአማረኛችንን ጥንካሬ ለማሳየት የሚችል ይመስለኛል፡፡ ለዚህም እንደምክንያት የማቀርበው መበረታታትም ሆነ መነቃቃትን በአንድ ላይ አዝሎ ማሳየት የሚችል አቅም ያለው ቃል በመሆኑ ነው፡፡

...ወዳጆች እስኪ የሚያበረታታንን ሰውም ሆነ ሃሳብ በማጣት እንደ ግለሰብም ሆነ እንደ ሃገር ያጣናቸውን ነገሮች እናስብ… እልፍ አይሆኑምን? በተለይ እንደ ብርድልብስ የተከናነብነው መፋዘዝ የሞቀን፣ እንደ ፍራሽ የተኛንበት ቸለኝተኛነት እና እንደማክዳ የተንተራስነው ግለኝነት የተመቸን፣ እንደ መብራትም ያጠፋነው አስተዋይነት ያዘጋጀን፣ ወዘተ እና ወዘተ አይነት ሆኖ እንቅልፍ ብቻ የመረጥን መስሎ አይሰማችሁም?
…እስቲ እንቀሳቀስ መንቀሳቀሱንስ የተካንበት ይመስላል… ሃገር ውስጥ ተፍተፍ እውጪም ተፍተፍ… እንደውም በታሪካችን ከምንግዝውም በላይ በውስጥም በውጪ እየተንቀሳቀስን አይሆንም ብላችሁ ነው…

እናም ይህ ጥሪ በንቃት እንንቀሳቀስ ዘንድ እንድንቀሳቀስ ነው! … ተንጠራራን ማለት ነው… 
ለንቃት…፡፡

ሰላም!